No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Monday 13 August 2012

መነገር ያለበት ቁጥር ሁለት! በልጅግ ዓሊ

አብደላ ኦጀላን(Abdullah Ocalan) የኩርዲስታን የሠራተኛ ፓርቲ (Kurdistan Workers’ Party) መሪ ነበር። ይህ ግለሰብ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1999 ኬንያ ውስጥ ተይዞ ዓይኑ በእራፊ ጨርቅ ተሸፍኖ፣ ሁለት እጆቹ ታስረው ወደ ቱርክ ሲወሰድ በዓለም የዜና ማሰራጫ በወቅቱ ታይቷል። በአሁኑ ወቅት አብደላ በቱርክ መንግሥት የዕድሜ ልክ ፍርድ ተበይኖበት ለብቻው በአንድ ደሴት ላይ ታስሮ ይገኛል።
አብደላ ከመታሰሩ በፊት ድርጅቱን የሚመራው ከኩርድ ሕዝብና ጦር ተለይቶ ሶርያ ውሰጥ ሆኖ ነበር። የኩርዶች ትግል በጠነከረ ወቅት የቱርክ መንግሥት፣ ሲ.አይ. ኤና ሞሳድ በመተባበር ይህንን ድርጅት ለማጥፋት ይታገሉ ጀመር። በሶርያ መንግሥት ላይ ባደረጉት ተጽዕኖ ከሶርያ እንዲወጣ ተደረገ። የቱርክ ጠላት ነች የምትባለውም ግሪክ አልቀበልም አለች። መጨረሻ ኬንያ ሃገር እንዲሄድ ተደርጎ በቱርክ የደህንነት ድርጅት አባሎች ተይዞ ቱርክ ውስጥ ታሰረ። በዚያ ወቅት የሚከላከልለት ጦር፣ የሚደብቀው ሕዝብ አላገኘም። አንድ መሪ ከሚመራው ሕዝብ ከተለየ ከባሕሩ የወጣ ዓሣ ነው የሚሆነው። ከምትመራው ሕዝብ ተነጠለህ የሌላ ሃገር ጥገኝነትን አምነህ መሄድ የሚፈጥረው ችግር አንዱ ይህ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ጥገኝነት የጠየከውን መንግሥት ጥቅም እንድታስጠብቅ ትገደዳለህ። ከዚህ ሁሉ ተጽዕኖ ነጻ ለመውጣት አማራጩ ከሕዝብ ውስጥ መገኘት ነው። የምትመራው ሕዝብ ከወደደህ ይደብቅሃል። የምትመራው ሕዝብ ከጠላህ ያጋልጥሃል። ከዛስ አልፎ ከሕዝብህስ ጎን ሆነህ ብትሰዋ ከዛ የበለጠ ታላቅነት ምን አለና ነው?
በሕዝብህ ማህል መሆን ብዙ ጥቅም አለው። የሕዝብህን ችግር በሚገባ ታውቀዋለህ፣ መፍትሔውንም ትሻለህ። ለሌሎች ሃገሮች ተጽዕኖ በቀጥታ ተጠቂ አትሆንም። በሩቅ ሆነህ በድህረ ገጽ ላይ በእንግሊዘኛ ብትለቀልቅ፣ ታላላቅ ስብሰባ እየጠራህ ሳይንሳዊ ትንታኔ ብትሰጥ፣ የምትኖርበትን ሃገር ታሪክ እያጠናህ ብትጽፍ ብዙም ፋይዳ አታመጣም። የሚሰማህም ላይኖር ይችላል። ይበልጥ ትዳከማለህ። እርስ በእርስ እንደ አሜባ እየተከፋልክ ለሕዝብህ በሽታ ትሆናለህ።
ለዚህ መረጃ የሚሆንን በኢሕአፓ ይደረግ የነበረው የመሣሪያ ትግል በብተና ንቅናቄ አባላቱ ወደ ሱዳን ከተሰደዱ በኋላ ድርጅቱን ከውጭ ሆኖ ለማሰባሰብ የተደረገው ሙከራ በተለይም ከነ ጸጋዬ ደብተራው በወያኔ መታሰርና ከነ ጋይም መገደል በኋላ ሊያንሰራራ አልቻለም። በሌላ በኩል ደግሞ የቅንጅትን ሁኔታ እንደ መረጃ ልንወስድ እንችላለን። የቅንጅት እንቅስቃሴ ከተኮላሸ በኋላ በቅንጅት መሪዎች ከውጭ ሆነው ሕዝቡን ለመምራት ያደረጉት ሙከራ የበለጠ መከፋፈልን፣ የበለጠ አድርባይነትን ነው የወለደው። የቅንጅት ብቻ ሳይሆን በዚህ በጸረ ወያኔ ትግል ከውጭ ሆኖ ለመምራት የተደረገው ሙከራ ሁሉ የተለየ ዕጣ አልነበረውም።
በውጭ ተደራጅተው መታገል በሃገራችን ብቻ የተጀመረ አይደለም። በሌሎች ሃገሮችም ይደረጋል። ችግሩ ግን ከውጭ ተታግሎ ለድል የበቃ አይኖርም። በውጭ ያለው ትግል ምንአልባት በሃገር ውስጥ የሚደረገውን ትግል ያግዝ እንደሆን እንጂ ብቻውን ነጻነትን አያስገኝም። ነጻነትን የሚጎናጽፈው መስዋትነትን የሚጠይቅ የሃገር ውስጥ ትግል ብቻ ነው።
ሕዝባዊ ድል ሳይሆን ለሥልጣን መብቃት ግን ከመስዕዋትነት ውጭ ሊሆን እንደሚችል ደግሞ በቅርብ የተፈጸሙ ክስተቶች ያስተምሩናል። ሌሎች በሞቱበት፣ ሌሎች በደሙበት በመጨረሻው ሰዓት ላይ የድል አጥቢያ አርበኛ በመሆን በምዕራብያውያን ሚዲያ ተደግፈው ለሥልጣን መብቃት እንደሚቻል ግልጽ ሆኗል። ለምሳሌ ያህል የአፍጋኒስታኑ አህመድ ካርዛይ እና የኢራቅ መሪ አል ማላኪን መመልከት ይቻላል። የአሜሪካ መንግሥት ከተደበቁበት አውጥቶ ሌሎች በተሰውበት ትግል ለሥልጣን እንዲበቁ አድርጓቸዋል። ያም ቢሆን በአሜሪካ ጦር ተደግፈው ነው። የሚኖሩትም በአሜሪካ ጦር ጥላ ሥር ነው።
እነዚህ ከውጭ ተመርጠው ሥልጣን ላይ እንዲቀመጡ የተደረጉ ግለሰቦች ተመሳሳይ ጠባይ አላቸው። የራሳቸውን ሕዝብ መበደልና ለሥልጣን ያበቃቸውን መንግሥት ጥቅም ማስጠበቅ ነው ። ካርዛይ ዛሬ አፍጋኒስታን ውስጥ በአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች በአሸባሪ ስም ለሚሞቱት ንፁህ ዜጎቹ ለይምሰል ያህል መግለጫ ከመስጠት ያለፈ የሠራው የለም። የኢራቅ መሪዎች በየእስር ቤቶችቻው ውስጥ በአሜሪካ ወታደሮች የሚደርስውን ግፍ ደገፉ እንጂ አልተቃወሙም።
አሁን ባለው የሃገራችን የዴሞክራሲ ትግል ውስጥ ብዙ ካርዛይን፣ ብዙ አልማላኪ ለመሆን የሚያልሙ እንዳሉ ግልጽ ነው። ሌሎች በታገሉበት፣ ሌሎች በሞቱበት በአሥራ አንደኛው ሰዓት ሙሉ ልብስና ከራባታቸውን አድርገው ለሥልጣን ብቅ ማለትን የሚሹ እንዳሉ ይህንን የወያኔ ዘረኝነት ትግል ለተከታተለ የአደባባይ ምስጢር ነው። ይህንን ለማወቅ ለፈለገ ደግሞ <<የታላቅ ስብሰባ ጥሪ>> እየተባለ በሚበተነው ማስታወቂያ ላይ ከረባታቸውን አንጠልጥለው የቁንጅና ውድድር ይመስል የሚደረደሩትን ፖለቲከኞች ማጤን ነው። በፎቶው ላይ ከሚደረደሩት የድርጅት መሪዎች ብዛት አንጻር፣ የሚደረገውን ትግል ላጤነ፣ እውን ይህቺ ሃገር ይህ ሁሉ ታጋይ እያላት ነው እንዲህ በወያኔ ሕዝቡ የሚሰቃየው? ብሎ ቢጠይቅ አያስገርምም።
እነዚህ በዚህ ሃያ ዓመት ውስጥ በተለያየ ወቅት ስብሰባ እየተጠራላቸው የምነውቀውን እውነታ እንደገና በድጋሚ የሚደሰኩሩልን ግለሰቦች በአሁኑ ወቅት የመለስን <<ከዚህ ዓለም መለየት>> በሚመለከት ምን ያስቡ ይሆን? ብሎ መጠይቅ ደግሞ ወቅታዊ ጥያቄ ይሆናል።
መለስ የሥርዓቱ ቁንጮ ነውና መሞቱ ለውጥ ያመጣል ብለው የሚያምኑ ትንሽ አይደሉም። የወያኔን የዘር ፖለቲካንም ሆነ ኢሕአዴግን የሚቀበሉና መለስን እንደ ዋና ጠላታቸው የሚወስዱ ግለሰቦች ወይም ተቃዋሚ ድርጅቶች ትግላቸው ከመለስ መሞት ጋር ያከትማል። የተነሰቡበት ዓላማ ግለስባዊ ጥላቻ በመሆኑ መለስ ከሞተ ሌላ የሚዋጉት አይኖራቸውም። ስለዚህም ከወያኔ ተታርቀው ለመቀጠል ጥሩ አጋጣሚ ነው የሚሆንላቸው። የመሞዳሞድ አቅማቸውና ችሎታቸው እየታየ ወያኔ በፈቀደ ሥልጣን የሚያገኙ ይኖራሉ። ሌሎቹም ታማኝ ተቃዋሚ ሆነው የሚቀጥሉ ይገኙባቸዋል። የመለስ ተተኪዎችም ሁኔታው የተቃዋሚውን ጎራ ስለሚከፋፍልላቸው በደስታ ይቀበሏቸዋል። እነዚህ ወደ ታማኝ ተቃዋሚነት የተቀየሩ ድርጅቶች <<አሁን መለስ ሞቷልና ሰላማዊውን ትግል እናጧጡፍ>> ቢሉን የሚጠበቅ እንጂ የሚገርም አይሆንም። ከእነርሱም ጋር የትግሉ መርዘም ያንገፈገፋቸው ወያኔን ለመደባለቅ ጥሩ አጋጣሚ ይሆንላቸዋልና ትግላቸው እዚህ ላይ ሊያከትም ይችላል፡፡ይህ በተቃዋሚው ድርጅት መካከል ከመለስ በኋላ የመጀመሪውን አዲስ ክፍፍል ሊፈጥር ይችላል።
አንዳንድ የዋሆች መለስ በመወገዱ ብቻ ወያኔ ተንኳታኩቶ ይወድቃል ብለው የሚያስቡ ይኖራሉ። ያ እንደማይሆን ግን ግልጽ ነው። ምን አልባት የመለስ መሞት የሚፈጥረው የውስጥ ክፍፍልን ሊሆን ይችላል። በዚህም ምክንያት ወያኔ መዳከሙ አይቀርም። ይህንን የደከመ መንግሥት በምን ዓይነት መንገድ ማስወገድ ይቻላል? የሚለው ጥያቄ ጎልቶ ስለሚወጣ ማየቱ ጥሩ ነው። በሁለት ዓይነት መንገድ ሊወገድ ይችላል።
1ኛ. በታጠቀ ኃይል
አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የወያኔን ጦር አንበርክኮ ለሥልጣን የሚበቃ የታጠቀ ኃይል አልታየም። ስለዚህ ይህ ኃይል ተጠናክሮ ለሥልጣን ለመብቃት የመለስ ሞት ብቻ በቂ አይደለም። አንዳንድ ፖለቲከኞች በኤርትራ ተረድተን በትጥቅ ትግል ወያኔን እንጥላለን ብለው የሚያስቡ አሉ። ይህ ጉዳይ በተደጋጋሚ በተለያዩ ግለሰቦች ተሞክሮ የከሸፈ ነው። አደገኝነቱንም መጤን ያስፈልጋል።
ተስፋዬ ገብረአብ( ግብረ እባብ) የመለስ ሞትን አስመልክቶ እንደሚያቀነቅነው <<በኤርትራ የሚደገፉት ተስፋ አላቸው>> የሚለው የሻዕብያ መልዕክት እንደሆነ ማመን ይኖርብናል። ይህ ከሆነ ሻዕብያ ለተለያዩ ተቃዋሚዎች አሁን እንደሚደርገው እያስታጠቀ የእርስ በእርስ ጦርነት ለማስጀመር ይጥር ይሆናል። አንዳንድ የዋሆች ኢሳያስን አምንው ከላይ የጠቀስኩት የአብደላ ኦጀላን እጣ እንዳይገጥማቸው ነው። ወያኔ በኤርትራ በኩል ውጥረቱ ከበዛበት ሻዕብያን በጦርነት አስፈራርቶ ተቃዋሚዎች ለመረከብ ጥረት ማድረጉ አይቀርም። አሁን ባለው የኃይል መጠን ደግሞ የኤርትራ መንግሥት ጦርነት ለመግጠም ፍላጎት የለውም። የተስፋዬ ግብረ እባብ አባባል ከልብ ማጥናት ያስፈልጋል።
2ኛ በሕዝባዊ አብዮት
በአሁኑ ወቅት አብዮት በሃገራችን ሊነሳ ይችላል።የዴሞክራሲ እጦት፣ በዘር በጎሳ መከፋፈል ፣ የሃይማኖት ነጻነት ማጣት( በእስልምና ኃይማኖት ተከታይ ወንድሞቻችን ላይ የሚደረገው እንቅስቃሴ ፣ የዋልድባ ገዳም ላይ እየደረሰ ያለው ግፍ እና ሌሎችም) ኤኮኖሚው፣ በነጻው ፕረስ ላይ የሚደረገው ግፍ፣ በተለይ በሕዝብ ላይ ወያኔ የሚያደርስው ቅጥ ያጣ ግፍ. . . ወዘተ . . . ከመለስ መሞት ጋር ተያይዞ ለውጥን ሊጠራ ይችላል። በሃገሪቱ ውስጥ አብዮት መነሳት ይችላል ብለን ካመንን ይህንን አብዮት ማን ይመራዋል ? የሚለው ጥያቄ ደግሞ መመለስ አለበት።
አሁን ከምንገነዘበው አብዮት ሃገሪቱ ውስጥ ቢነሳ በተቃዋሚዎች በኩል ቅድመ ዝግጅቱ እየተደረገ አይደለም። ተቃዋሚዎች ይበልጥ የሕዝብ ጥያቄ የሆነውን የኅብረት ጥያቄ በትምክህት አሻፈረኝ በማለት የድርጅትን ዝናን፣ የግል ታዋቂነትን የሚቀነቅኑ ሆነው እናገኛቸዋለን።
በአሁኑ ወቅት ተፈጠሩ የተባሉትም ሕብረቶች ወይም ጥምረቶች የይስሙላ ብቻ ናቸው። በውስጣቸውም የሚገኙት ድርጅቶች አባል የሌላቸው፣ ለመሪዎቻው ስም ማስጠሪያ ብቻ የተሰፉ ቁናዎች ሆነው እናገኛቸዋለን። እንዲውም ብዙዎቹ በሃገራችን ውስጥ ቀርቶ በሚኖሩበት ሃገርም ታዋቂነትም ተቀባይነትም የላቸውም።
አስረጅ ፡ http://ethiomedia.com/2012_report/joint_memorandum.pdf
ይህ አዲስ ትብብር ፈጠርን ብለው ከተደረደሩት ድርጅቶች ስንቶቹን ነው አጥርተን የምናውቃቸው? ስንቶቹስ በሃገራችን ውስጥ እንቅስቃሴ ያደርጋሉ? እነዚህ ለቁጥር ማብዣ ሲባል የተደረደሩ ድርጅቶች ራስን ከማታለል የማያልፍ ብልጠት ነው።
በውጭ የሚገኙትን ትተን በሃገር ቤት የሚገኙትን ድርጅቶች ስንመዝናቸው በደረሰባቸው የወያኔ ጭቆናና ጠንካራ መሪ በማጣት ብዙዎቹ የተካፋፈሉና ወደፊትም ገና ከመለስ ሞት በኋላ የሚከፋፈሉ ሆነው እናገኛቸዋለን። አንዳንዶቹ ሕዝባዊ አብዮትን ለመምራት ጉልበቱም ፍላጎቱም የሌላቸው መሪዎች በውስጣቸው አሉ። አንዳንዶቹ ጥገናዊ እንጂ መሠረታዊ ለውጥም አይፈልጉም። እነዚህ ግለሰቦች አብዮቱን ከመምራት ወደ ማክሸፍ ሊሸጋገሩ ይችላሉ። ይህ አብዮትን የማፈን እንቅስቃሴ ከ 97 ምርጫ ወቅት የሙት ከተማ ንቅናቄ የተመለከትነው ስለሆነ ዛሬ አዲስ አይሆንም። የውጭ መንግሥታትና ቆራጥ ያልሆኑ አመራሮች እንዴት እንዳከሸፉት የምናስታውስው ነው። በሃገር ውስጥ ስለሚገኙ ነባር መሪዎች <<ፍኖተ ነፃነት>> ሁለተኛ ዓመት ቅጽ 2 ቁጥር 54 ገጽ 7 <<የማይጠረቃው የተቃዋሚ ፓርቲዎች ትግልና የሃገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ>> —- በቀለሙ ሁነኛው ማንበብ ጠቃሚ ነው።
http://ethiomedia.com/2012_report/fnote_fifty_four.pdf

በውጭ የሚገኙትን ድርጅቶች ደግሞ ይህንን ይነሳል ብለን የምንጠብቀውን አብዮት ከውጭ ሆነው መምራት ስለማይችሉ ሃገር ውስጥ ካሉት ጋር በመተባበር ለመምራት መሞከር እንዱ አማራጫቸው ሊሆን ይችላል። ያ ደግሞ ብዙም የሚያወላዳ አይደለም። እንደሚታወቀው ተባብሮ ለዴሞክራሲ መታገልን ለሃያ አመታት አሻፈረኝ ስላሉና አሁን በመጨረሻ ሰዓትም ኅብረት ቢፈጥሩም ኅብረቱ የሚገፋ አይሆንም። ከዚህ ቀደሞ በቅንጅት እንደታየው በትንንሹም ጉዳይ እየተከፋፈሉ ሊጣሉ ይችላሉ።
ተቃዋሚዎች በራሳቸው መፍትሄ የማያመጡ ከሆነ ያላቸው አማራጭ በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ በሶርያ እንደታየው የምዕራብያውን ቡራኬ መጠበቅ ነው። ሃገራችን ውስጥ አብዮት ከተነሳና ወያኔ መወገድ ካለበት አብዮቱን በውጭ ያሉ ድርጅቶች ተከፋፍለው መምራት የማችሉ ስለሆነ የውጭ መንግሥታት እንደተለመደው የሽግግር መንግሥት ለማቋቋም ጥረት ያደርጉ ይሆናል። በዚህ ወቅት አባላት የሌላቸው ድርጅቶቻቸውን ታቅፈው ካለ ምንም እንቅስቃሴ ራሳቸው ብቻ እያስተዋወቁ ይጠብቁ የነበሩ ፖለቲከኞች የትግላቸውን ፍሬ የሚሰበስቡበት ቀን ደረሰ ማለት ነው። በዚህ ወቅት እንደተለመደው መሪዎቹ ከረባታቸውን አድርገው ብቅ ከማለት አይቆጠቡም። ስሞኑን የሚታየው የአትርሱኝ ባይነትም የሚመስለው መግለጫም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ሊሆን ይችላል።
ይህ በውጭ መንግሥታት የሚደረገው ጥረት ከተሳካ ድርጅቶቹ የተከፋፈሉ ስለሆኑ የአንዱ ድርጅት መሪ እንደ አማራጭ ለሚፈጠረው ኅብረት መሪ መሆን ችግር ሊፈጥር ስለሚችል የድርጅት አበል ያልሆነ፣ ከማንም ያልወገነ ግን በፓለቲካው ጎልቶ የሚታይ ምሁር ሊያስፈልግ ነው ማለት ነው።
እዚህ ላይ ነው የሚቀጥለው የኢትዮጵያ ካራዛይ ማነው? የሚለው ጥያቄ የሚጀምረው።
እንደ አፍጋኑ መሪ ካርዛይ በእንግሊዘኛ የጎለበተ፣ የአሜሪካንን ታላቅነት የተቀበለ፣ የእነርሱን ባሕል የወረሰ ቢሆን ደግሞ አሜሪካኖች ስለሚያስደስታቸው ምርጫቸውን ያውቁታል ማለት ነው። እሁን ከምናየው አንዳንድ ምልክቶቻቸው ቀደም ብለው የተዘጋጁበት ይመስላል።
ዛሬ በዚህ ትግል ውስጥ ካርዛዩች ትንሽ አይደሉም። እነርሱ ባልሞቱበት፣ እነርሱ ባልቆሰሉበት፣ እነርሱ ባልታሰሩበት የይስሙላ ድርጅት እያቋቋሙ በሕብረት ስም ወደ ሥልጣን ለመጓዝ የሚደረገው ጥረት በዚህ ሃያ ዓመት ውስጥ የኋልዮሽ ግልቢያ እንጂ የረባ ትግል አላሳየንም። ይህንን ትግል አሽመድምደው የወረቀት ላይ ነብር ያደረጉት በባዶ ለስልጣን የቋመጡ ብኩን የይስሙላ ድርጅት መሪዎች ናቸው።
ግማሾቹ ትግሉን ሳይጀምሩት የዲፕሎማቲክ ግንኙነት ከውጭ መንግሥትታት ይጠይቁ ጀምረዋል። የሃገራቸው ሕዝብ የትግላቸውን ጥረትና ውጤት ተመልክቶ እውቅና ሳይሰጣቸው በውጭ መንግሥት ቡራኬ ለማግኘት ጠዋት ማታ የአሜሪካንን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤትንና እጅ መንሳት ከተጀመረ ሰንበትበት ቢልም ሰሞኑን መለስ ታመመ ! መለስ ሞተ ! መለስን ማነው የሚተካው ? የሚለው ጥያቄ መንገዋለል ከጀመረ ጀምሮ ደጅ ጥናቱ እንደጎላ እየተሰማ ነው።
ይህ ግን የኢትዮጵያን ሕዝብ ነጻ አያወጣውም። በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ አሁንም በሶርያ እንደምንመለከተው ከሕዝብ ችግር ተለይቶ፣ ለውጭ ባሕል ተገዝቶ፣ ለውጭ ሃገር ታላቅነት የሚሠራ መሪ የሃገራችንን ገበሬ ልጁን እየነጠቀ ወደ ሶማሊያ በመላክ ያስገድልበት እንደሆን እንጂ ችግሩን አያቃልለትም። ለሠራተኛውም ቢሆን ከዓለም አቀፍ ድርጅቶች የሚቀርብለት ጥያቄ ለመመለስ ያህል ከሥራ ያባርረው እንደሆን እንጂ መብቱን አያስጠብቅለትም። በኢራቅ እንደተመለከትነው አዳዲስ እስር ቤቶች ያሰራ እንደሆን እንጂ ያሉትን አያፈርስም። በሊቢያ ፣ በሶርያ እንደተመለከትነው በዘር፣ በሃይማኖት ከፋፍሎ ያጋድል እንደሆን እንጂ ከወያኔ የግፍ አገዛዝ አላቆ ዴሞክራሲያዊ ሃገር አይመስርትም።
ለዚህ ሁሉ መፍትሄው አንድ ነው። በሃገራችን ውስጥ ያሉ ፖለቲከኞች የወቅቱን ሁኔታ በመገንዘብና፣ ከቀን ወደ ቀን ሕጋዊ ሆኖ መንቀሳቀሱ አደገኛነቱን በማጥናት፣ ሌላ ዘዴ ዛሬውኑ መተለም ይኖርባቸዋል። እየተዘጉ የሚገኙትን ጋዜጦች የሚተካ የህቡዕ ጋዜጣ ማዘጋጀት አስፈላጊ ነው። ልንተማመንበት የምንችለውን ሕዝብ በሕቡዕ ማሰባሰብ አስፈላጊ ነው። በሕዕቡ ሆኖ የሕዝብን አብዮት መምራት የሚቸል ኃይል እዛው ሃገር ውስጥ መቋቋም ይኖርበታል። ተዘጋጅተን ከጠብቅን ብቻ ነው ገዥዎቻችንን ሌሎች የማይመድቡብንና መሪዎቻችንን ራሳችን የምንመርጠው ፣ ስንደራጅ ብቻ ነው ወያኔን የምንጥለውና የሚቀጥለውን መንግሥት የሕዝብ የምናደርገው። ሕዝብ መሃል ስንሆን ነው የሕዝብን ችግር የምረዳው።
<<ይህ ሃገር የኛም ነው>> በሚል መፈክር እዛው ሃገራችን ውስጥ የሚፈጠር እንቅስቀሴ እንጂ ፣ ሙሉ ልብስና ከረባትን አሳምሮ በዓለም ታላላቅ ከተማዎች ውስጥ የሚደሰኮር (ከፍትህ አምደኛ በድሉ ዋቅጅራ ይህንን ቃል ልዋሰውና) አማርዝኛ (አማርኛ + እንግሊዝኛ ) መፍትሄ ያመጣል ብለን ማመንን ከሃያ ዓመት በኋላ ማክተሙን ካላመንን መቼ ልናምን ነው።
በውጭ የሚገኘውም ኢትዮጵያዊ ከወያኔ ጥርስ ተናክሰው ዛሬ በየእስር ቤቱ የሚማቅቁትንና የሚታገሉትን በተቻለው መጠን መርዳት ሲገባው፣ ለሚቀጥለው ካርዛይነት ለሚታገሉ ባለ ከረባት የፖለቲካ ተንታኞች ዲስኩራቸውን የሚያሰሙበት ምርጥ አዳራሽ ፣ የአውሮፕላን ቲኬትና ምርጥ መኪና ማዘጋጀት መቼ ነው የሚያከትመው። እነዚህ የየስሙላ ታጋዮች ትተን ስለ ሃገራቸው በማሰብ እውነትን በመጻፋቸው በእስር ቤቱ ለሚማቅቁ ጋዜጠኞች ቤተሰብ እርዳታን ስናደርግ ብቻ ሌሎች ቆራጥ ታጋዮች እንዲፈጠሩ የምናበረታታው። በዚህ መንገድ ነው በእነዚህ ቆራጥ ታጋዮች የበሰለና ሃገራችንን ነጻ የሚወጣ ድርጅትም የሚፈጠረው፣ መከራችንን በቅርብ የሚያከትመው።
ጎበዝ እውነተኛ ትግልን ከፈለግን፣ የተቃዋሚ ድርጅት መሪዎች ድክምታቸውን መነገር አለበት። ሃያ አመት ኪሳችንን እያራቆትን፣ ተስፋ ባለ መቁረጥ ታገልን። ያገኘነው መከፋፈልልን፣ የባሰ ተስፋ መቁረጥን ነው። ከአሁን ወዲህ ግን << ይህ ሃገር የኛም ነው >> ብለው መከራን ከሚቀምሱት ጋር አብረን መቆም አለብን። በውጭ የሚገኙት ባለ ከረባቶችም ከዚህ በፊት በታሪክ እንዳየናቸው የኢትዮጵያ ቆራጥ ልጆች ወደ ሃገራቸው በሕብዑ በመመለስ ሲታገሉ ብቻ ነው ለውጥ ሊያመጡ የሚችሉትና ሃቀኛ መሪዎቻችን የሚሆኑት። ይህንን ደግሞ ልንነግራቸው ይገባል።
ዛሬ ሃገራችን ካለችበት አደገኛ ሁኔታ አንጻር ከውጭ ብቻ ለውጥ ለማምጣት የሚደረገው ትግል መቆም አለበት። ሕዝብ በውጭ ያሉ ድርጅቶች አንድ ቀን ነጻ ያወጡኛል ብሎ በተስፋ መጠበቅን አቁሞ እዛው ሃገራችን ውስጥ መፍትሄ መፈለግ የሚጀምረው እነዚህ የይስሙላ ድርጅቶች ሲያከትሙ ነው። በእነዚህ የይስሙላ ድርጅቶች ከርሰ መቃብ ላይ ሃቀኛ በሕዝብ ውስጥ ያለ ድርጅት እንዲመሰረት መታገል የሁላችንም ዓላማ መሆን አለበት።
እነዚህ የይስሙላ ሥልጣን ናፋቂ ድርጅቶች በሃገራችን አብዮት ቢነሳ አደገኝነታቸው የጎላ ነው። የኢትዮጰያ ሕዝብ እንደ ግብጽ ሕዝብ አንድ ላይ ሊቆም ይችላል። ግን አሁን ያሉት እርስ በእርስ በመጣላት የቆሰሉ ተቃዋሚ ድርጅትቶችና መሪዎቻቸው በአንድ ላይ ይቆማሉ ወይ? በአሁን በምናየው ሁኔታ ከሆነ ደግሞ በፍጹም እንደማይስማሙ እርግጠኞች ነን። ምንአልባትም የኤርትራን ዓላማ ለማስፈጸም የተነሱ ብዙ ስላሉ አብዮቱን ወደ እርስ በእርስ የጦርነት አውድማ ለመቀየር የሚጥሩም አይጠፉም።
ቀኑ ዛሬ ነውና ሃገራችንን በጠላቶቿ የተዘጋጀላትን ጥፋት ለመከላከል ከድርጅት ጎጆ በላይ ማሰብ ያስፈልጋል። በሚሆን በማይሆነው የተከፋፈሉ ድርጅቶች ይህንን ጥፋት ተመልክተው ቅራኔዎቻቸውን ለማስወገድ መጣር ይኖርባቸዋል። ይይስሙላ ድርጅቶች መክስም ይጠብቅባቸዋል ። . . . እነዚህና የመሳሰሉትን ካላደረግን በታሪክም ተወቃሽ ስቃያችንም የበዛ ዜጎች ሆነን እኖራለን ።
Beljig.ali@gmail.com
ይህች ሃገር የሁላችንም ነች !!!
ስለ ሃገራችን የሚያስብ ሁሉ ሰላም ይክረም!!!
በልጅግ ዓሊ

No comments:

Post a Comment