No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Monday 17 December 2012

ከእሁድ እስከ እሁድ (የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)

 
ገበያ የደራላት ጅቡቲ
ታህሳስ 4 ቀን 2005 ዓም ከወደአገርቤት የተዘገበው ዜና መለስን በማስታወሻነት የሚዘክር ሆኗል። ዜናው እንዳለው ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በተገኙበት ጅቡቲ ታጁራ ላይ  አዲስ ወደብ ለመገንባት የመሰረት ድንጋይ የማስቀመጥ ስነስርዓት አከናውናለች። የጅቡቲው ፕሬዝዳንት ኢስማኤል ኦማር ጌሌ  የወደቡ ግንባታ ሲጠናቀቅ ኢትዮጵያ የምትፈልገውን የወደብ አገልግሎት በተሟላ ደረጃ እንድታገኝ ያስችላታል ሲሉ የ “ገበያው ደራ” ንግግር አድርገዋል።
በስነ ስርአቱ ላይ የተገኙት ሃይለማርያም ደሳለኝ ፥ አዲሱ የወደብ ግንባታ የኢትዮጵያና የጅቡቲ ህዝብ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑንን ጠቅሰው መናገራቸውን የገለጸው ፋና ብሮድካስቲንግ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት በየብስና በባቡር ትራንስፖርት ፣ በሃይል አቅርቦትና በወደብ አገልግሎት የተቆራኘው የሁለቱ ሃገራት ግንኙነት በመልካም ደረጃ ላይ ይገኛል” ሲል
ለጅቡቲ ገበያ እጅ የሚነሳ ሪፖርት አቅርቧል። ኢትዮጵያ ተከራካሪ መሪ ስለሌላት ህጋዊ ወደቧን አጨብጭባና ደግሳ ካስረከበች በኋላ ተንፈራግጣ የምትሰበስበውን ምንዛሬ ለጅቡቲ እያስረከበችና ለዚሁ የታሪክ ጠባሳ የዳረጓትን አቶ መለስን “ባለራዕይ መሪ፣በብሄራዊ ጥቅም የማይደራደሩ እውነተኛ አባት” እያለች ትኖራለች፡፡
አርቲስት ህይወቴ አበበ አረፈች
ምክንያቱን ሳይገልጽ ኑሮዋን ኡጋንዳ አድርጋ እንደነበር ፋና ሬዲዮ ይፋ ሲያደርግ፣ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዘሎታል። ትውልዷ ሐረር ከተማ ሲሆን ባለትዳርና የአንዲት ልጅ እናት ነበረች። ሃረር አማተር ቲያትር የጀመረችውን ትወና ገፍታበት ለመጀመሪያ ጊዜ “ቀዝቃዛ ረመጥ” የሚለውን ቲያትር በመተወን ብሄራዊ ቲያትር መድረክ ላይ የታየችው በ1992 ነበር ወጣቷ የመድረክ ሰው ህይወቴ አበበ።
አስራ ሶስት ዓመት በቆየችበት የትወና ስራ ባለታክሲ፣ ውበትን ፍለጋ፣ የሰርጉ ዋዜማ፣ የመቃብር ቁልፎች፣ ባለቀለም ህልሞች፣ ሰውየው ወዘተ በተሰኙ ፊልሞችና ቲያትሮች ላይ ተጫውታለች። የ31 ዓመቷ አርቲስት ጳውሎስ ሆስፒታል በህክምና ስትረዳ ቆይታ ህይወቷ አልፏል። አርቲስቷ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በቲያትር ጥበብ የመጀመሪያ ዲግሪ አላት። የዝግጅት ክፍላችን ለቤተሰቦቿና ለአድናቂዎቿ መጽናናትን ይመኛል።
አቶ ጁነዲን ሳዶ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቦርድ ሰብሳቢነት ተነሱ
የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ጁነዲን ሳዶ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቦርድ ሰብሳቢነት ሹመታቸው መነሳታቸውን ኢሳት አስታወቀ። በቅርቡ በኦህዴድ ተካሂዶ በነበር ግምገማ ተራ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ የተወሰነባቸው አቶ ጁነዲንን የተኳቸውና ዩኒቨርስቲውን በቦርድ ሰብሳቢነት የተመደቡት የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተክለብርሀን መሆናቸው ታውቃል።
አቶ ጁነዲን ባለቤታቸው በሽብርተኝነት ወንጀል ተከሰው መታሰራቸውን በመቃወም አንድ ጽሁፍ በግል ጋዜጣ ላይ ማውጣታቸው ይታወቃል፡፡ ይህ ጽሁፍ ከስልጣናቸው ለመባረራቸው ምክንያት መሆኑን የመንግስት ቃልአቀባይ አቶ ሽመልስ ከማል በአንድ ጋዜጣ ላይ ገልጸው ነበር። የኢትዮጵያ መንግስት፣ ከሳውዲው ቢሊየነር ሼክ ሙሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲን እንዲሁም ከሳውዲ መንግስት ጋር በቅርብ እየሰራ ወ/ሮ ሀቢባ ከሳውዲ ኤምባሲ ገንዘብ በመቀበላቸው እንዴት ሽብርተኛ ሊባሉ ይችላሉ በማለት ጥያቄ ያቀረቡ፣ የአቶ ጁነዲን ደጋፊ የሆኑ የኦህዴድ አባላትም በተመሳሳይ ከሀላፊነታቸው እየተነሱ እንደሆነ ኢሳት ታህሳስ 4 ቀን 2005 ዓ ም ዘግቧል። የኢትዮጵያ መንግስት እስካሁን የሳውዲ አረብያን መንግስትና የሳውዲ አረብያን ኤምባሲ ሽብረተኝነትን በማስፋፋት ወንጀል ሲከሳቸው አለመሰማቱንም ኢሳት አመልክቷል።
ኤርትራ 18 ለ 6 ትመራለች
ኤርትራና ኢትዮጵያ በ2012 ጋዜጠኞችን በማሰር ከአፍሪካ ከፍተኛውን ቁጥር እንደያዙ የአሜሪካ ራዲዮ ሲፒጄን ጠቅሶ ዘግቧል። በዓመቱ በአስራ አንድ ወራት 232 ጸሃፊዎች፣ የፎቶ ጋዜጠኞች እና የህትመት አዘጋጆች ታስረዋል። ኢራን፣ ቱርክና ቻይናን በደረጃ ያስቀመጠው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች  በአፍሪካ አርባ አራት ጋዜጠኞች ታሥረዋል ብሏል። ኢትዮጵያ ደግሞ ስድስት ጋዜጠኞችን፡፡ ኤርትራ ሃያ ስምንት ጋዜጠኞችን አስራ ለወራትና ለዓመታት ያስቀመጠችው ያለክስና ያለፍርድ መሆኑን አመልክቷል።
ኤርትራ ያሰረቻቸው ጋዜጠኞች ምሥጢራዊ እሥር ቤቶች ውስጥ በመሆናቸው ያሉበት ሁኔታ እንደማይታወቅ ያስረዳው ሲፒጄ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ መንግሥቱ ጋዜጠኞችንና ተቃዋሚዎችን ለማሠር በሽብር ፈጠራ ላይ የተከፈተውን ጦርነት እንደሽፋን ተጠቅሞበታል ሲል የተለመደና የሚታወቀውን ምክንያት ጠቁማል። የሲፒጄው መሐመድ ኬይታ እንዳሉት “የሽብር ሕግ” የሚለውን የብዥታ አጠራር ጋዜጠኞችንና ተቃዋሚዎችን በደፈናው ለመፈረጅ ጉዳይ ውሏል።
“የሃይለማርያም ካርድ”
የመለስንና የሃይለማርያምን መንገድ በማጣቀስ በፖለቲካ ገጹ ሰፊ ዘገባ ያቀረበው ሪፖርተር ፣ሃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት በይፋ እንዳይሰራጭ የሞገድ አፈና ካደረገበት አልጃዚራ ቴሌቪዥን ጋር ያደረጉትን ቃለምልልስ አስመልክቶ “ውህደት” የምትለውን ሃረግ በመጎተት የ“ሃይለማርያም የፖለቲካ ካርድ” ሲል አስተያየት አስፍሯል።
“ለእኛ ዋነኛ ጉዳያችን ድህነትን መዋጋት ነው፡፡ እንዲሁም ደግሞ አካባቢያዊ ውህደት መፍጠር፡፡ ሁለታችን ይህንን ማድረግ ከቻልን ምርታማ እንሆናለን፤” በማለትም አክለው ተናግረዋል፡፡ ድህነትን በተመለከተ በአብዛኛው የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም አስተያየት አሁንም በመለስ አቋሞች ላይ ያጠነጠነ ቢመስልም፣ “ውህደት መፍጠር ከቻልን” የሚለው ግን አዲስ “መላ” ይመስላል፡፡ “ውህደት መፍጠር” የሚለው ንግግር አቶ መለስ አንስተውት የማያውቁት ርዕሰ ጉዳይ ሲሆን፣ አንድ አዲስ ምዕራፍ አመላካች ሊሆን ይችላል የሚል ትንታኔ እየተሰጠበት ነው እንደሆነ ሪፖርተር ጠቁሟል።
ምናልባትም ሐሳባቸው በፕሬዚዳንት ኢሳያስ ተቀባይነት የሚያገኝ ከሆነ፣ ከአሥር ዓመታት በላይ የዘለቀው የሁለቱም አገሮች “ሰላምና ጦርነት አልባው” ግንኙነት መልኩን በመቀየር አዲስ ታሪክ ያስመዘገባል እየተባለ ነው፡፡ አገራቸው ውስጥ ባለው ሁኔታ ተቀባይነት ያጡትን ፕሬዚዳንት ኢሳያስም ምናልባት ከገቡበት ጥልቅ አዘቅት ውስጥ ሊያወጣቸው ይችላል፡፡ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምም፣ በኢትዮጵያዊያን ዘንድ የበለጠ ተቀባይነት ለማግኘት ሊጠቀሙበት የሚገባ የፖለቲካ ካርድ ሊሆን እንደሚችል የፖለቲካ ተንታኞች መናገራቸውን ሪፖርተር ታህሳስ 5 ቀን 2005 አስነብቧል።
ተቋርጦ የነበረው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ክስ እንደገና ተጀመረ
ዋስትና ተፈቅዶለት በ50 ሺሕ ብር ዋስ ተለቀቀ
ሦስት ክሶች ተመሥርተውበትና ዋስትና ተከልክሎ ለአራት ቀናት በማረሚያ ቤት ከቆየ በኋላ፣ ክሱ ተቋርጦ በነፃ የተሰናበተው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፣ የተቋረጠው ክስ በድጋሚ ትናንትና ፍርድ ቤት ቀርቦበት በ50 ሺሕ ብር ዋስ ተለቀቀ፡፡ ከነሐሴ 23 ቀን 2003 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት በፍትሕ ጋዜጣ ላይ በራሱና በጽሑፍ አቅራቢዎች አምስት ጊዜያት ታትመው በወጡ መጣጥፎች ምክንያት ክስ ተመሥርቶበት፣ ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም. የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 16ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ ዋስትና በመከልከሉ ማረሚያ ቤት እንዲቆይ መደረጉ ይታወሳል፡፡
ክስ መሥርቶበት የነበረው የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ፣ ‹‹የማጣራው ምርመራ ስላለኝ እስከዚያው ድረስ ክሴን አቋርጫለሁ፤›› በማለት ነሐሴ 21 ቀን 2004 ዓ.ም. ለፍርድ ቤቱ በጻፈው ደብዳቤ አማካይነት፣ ጋዜጠኛ ተመስገን ነሐሴ 22 ቀን 2004 ዓ.ም. ከእስር ተፈትቶ ነበር፡፡ ዓቃቤ ሕግ ላለፉት ሦስት ወራት አቋርጦት በድጋሚ በተንቀሳቀሰው ክስ ውስጥ ጋዜጠኛ ተመስገን በተለያዩ ጊዜያት ዕትሞች ‹‹ሞት የማይፈሩ ወጣቶች፣ የብሔር ብሔረሰቦች ቀን እስከ መጨፈር፣ የሁለተኛ ዜግነት ሕይወት እስከመቼና ሲኖዶስና መጅሊስ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ማጥመቂያ›› የሚሉ መጣጥፎች ማወጣቱ ተገልጿል፡፡
በመሆኑም በወጡት መጣጥፎች ወጣቶችን ለአመፅ አነሳስቷል፣ ቀስቅሷል፣ ስም አጥፍቷል በሚል ነበር የመጀመሪያው ክስ የቀረበው፡፡ አሁንም የቀረበው ክስ ይኼው ነው፡፡
በትናንትናው ዕለት ዓቃቤ ሕግ ለምን ክሱን ማንቀሳቀስ እንደፈለገ እንዲያስረዳ ችሎቱ ጠይቆት፣ ፍትሕ ሚኒስቴር በአዋጅ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ክስን የማቋረጥና የመጀመር ሥልጣን እንዳልው ከመግለጽ ባለፈ በዝርዝር አላስረዳም፡፡ ፍርድ ቤቱ በሁለተኛነት ክስ የተመሠረተበትና የፍትሕ አሳታሚ የሆነው ማስተዋል የሕትመትና የማስታወቂያ ድርጅትም እንዲቀርብ አዞ፣ ክሱ መቀጠል አለመቀጠሉን በሚመለከት ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ፍትሕ ጋዜጣ ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም. ለሕትመት ወደ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት የገባ ቢሆንም፣ ‹‹ፍትሕ ሚኒስቴር እንዳታትም ብሎኛል›› በሚል ምክንያት ማተሚያ ቤቱ አላትምም ማለቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ጋዜጣው በወቅቱ ለምን እንዳልታተመ እስካሁን በግልጽ የተገለጸ ነገር ባይኖርም፣ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በነበሩት በአቶ መለስ ዜናዊ ሕመምና በአጠቃላይ በወቅቱ ስለነበሩበት ሁኔታዎች የሚያትት መጣጥፍ ይዞ ስለነበር፣ ሕዝብን አላስፈላጊ ውዥንብር ውስጥ ይከታል በሚል ተሰግቶ መሆኑን የሚናገሩ አሉ፡፡ ጋዜጣው ከዚያን ጊዜ አንስቶ ተዘግቶ የቆየ ቢሆንም፣ ጋዜጠኛ ተመስገን በማኔጂንግ ኤዲተርነት ‹‹አዲስ ታይምስ›› በሚባል መጽሔት ላይ እየሠራ ይገኛል፡፡(በታምሩ ጽጌ – ሪፖርተር)
ሞቃዲሾ የአጥፍቶ ጠፊ ፈንጂ ጥቃት ደረሰባት
ተሽከርካሪ ላይ ፈንጂ ያጠመደ አጥፍቶ ጠፊ ሞቃዲሾ ዉስጥ ራሱንና የሌሎች ሶስት ሰዎችን ህይወት ማጥፋቱን የጀርመን የዜና ወኪል ከስፍራዉ ዘገበ። ሌሎች ስድትስ ሰዎችም በፍንዳታዉ መጎዳታቸዉን ዘገባዉ አመልክቷል።
በአጀብ የሚጓዙ የአፍሪቃ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ወታደሮችን ለማጥቃት ያለመዉ አጥፍቶ ጠፊ ኢላማዉን ስቶ መንገድ ዳር የቆሙ ሰዎችን መጉዳቱን ዘገባዉ ጨምሮ ገልጿል። አንድ የሶማሊያ ፖሊስ ባለስልጣን ደግሞ በበኩላቸዉ አጥፍቶ ጠፊዉ ከራሱ በቀር ሌሎች ሰዎች ላይ ጉዳት እንዳላደረሰ ነዉ ለአሶሺየትድ ፕረስ የገለፁት። ከሶስተኛ ወገን እስካሁን የተሰማ ማረጋገጫ የለም። ለጥቃቱ አልሸባብ ተጠያቂ መሆኑ ተገልጿል።
 ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (http://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

No comments:

Post a Comment