No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Tuesday 18 September 2012

በረከት ስምዖን ሕወሓቶችን ማባበል ይዘዋል


Share0

አቶ በረከት ስምዖን በአቶ መለስ ዜናዊ ሞት ላይ እንዲህ ቢያለቅሱም፤ በሕወሓቶች ዘንድ ግን “የአዞ እንባ” ነው በሚል ጥርስ ውስጥ ገብተዋል።

(ዘ-ሐበሻ) ለሕወሓቶች ስልጣን ማጣት ተጠያቂው በረከት ነው በሚል ጥርስ እንደተነከሰበት የሚነገርለት አቶ በረከት ስምዖን ሕወሓቶችን በየሚዲያው ላይ መግለጫ በመስጠት በማባበልና በመለማመጥ ላይ እንደሚገኝ ታወቀ። አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ እና አቶ ደመቀ መኮንን ስልጣኑን በኢሕአዴግ ውስጥ ያለውን ስልጣን ከያዙ በኋላ አንዳንድ የሕወሓት ሰዎች በሚድያ ላይ በስልጣን ሽግግሩ የተደሰቱ ለመምሰል ቢሞክሩም ውስጥ ለውስጥ ግን በከፍተኛ ቅራኔ ውስጥ ይገኛሉ። አቶ በረከት ሕወሓቶችን ለመለማመጥ ለሰንደቅ ጋዜጣ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ “ህወሓት የታጋለው የህወሓትን ስርወ መንግስት ለመፍጠር ሳይሆን ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመፍጠር ነው” በማለት ለማባበል ሞክረዋል። ሙሉ ቃለ ምልልሱን ይንብቡት።

አርብ እና ቅዳሜ (መስከረም 5 እና 6 ቀን 2005 ዓ.ም) ባካሄደው ጉባኤ በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ምትክ የግንባሩን አመራሮች መርጧል። በአመራር ምርጫውም የደኢህዴን ሊቀመንበር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የግንባሩ ሊቀመንበር ሆነው ሲመረጡ፤ የብአዴን ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ደመቀ መኮንን ደግሞ የግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል።
የአመራር ምርጫውን አካሄድና ምርጫውን ተከትሎ ስላሉት የተለያዩ አስተያየቶች እንዲሁም በጥቂት ሀገራዊ ርዕሰ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትርና የኢህአዴግ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል የሆኑትን አቶ በረከት ስምኦንን ባልደረባችን ዘሪሁን ሙሉጌታ በቴሌፎን አነጋግሯቸዋል።
ሰንደቅ፡- ከሰሞኑ የተካሄደው የኢህአዴግ ም/ቤት ስብሰባ አቶ መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት ከመለየታቸው በፊት ትተውት ባለፉት ሰነድ የአመራር መተካካቱ መፈፀሙ ተነግሯል። ይሄ ሰነድ ምንድነው?
አቶ በረከት፡- አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ወቅት በድርጅታችን ታሪክ ውስጥ ብዙ ሰነድ ነው ያዘጋጁት። ብዙ የትንተና ማቴሪያሎች አዘጋጅተዋል። አሁን ደግሞ በመጨረሻ የድርጅት ግንባታ አመራራችንን የሚመለከት ከዚህ በፊት በተለያዩ ሰነዶች ውስጥ ያቀረቧቸውን አሰባስበው ይበልጥ አዳብረው ያቀረቡት ሰነድ አለ። በእርግጥ ይሄንን ሰነድ ያዘጋጁት ለአሁኑ ምርጫ አስበው አይደለም። ኢህአዴግ በጠቅላላ በሀገር ደረጃ ብቃት ያለው ኢትዮጵያን የሚለውጥ አመራር እየገነባ እንዲሄድና እስካሁን የመጣበትን የትግል መድረክ አጠናክሮ ወደፊትም በዚህ ደረጃ የሚጠብቀውን ፈተናዎች ሁሉ በድል አድራጊነት እየተወጣ እንዲሄድና ድርጅቱም የአመራር አቅም እየኮተኮተ እንዴት ይቀጥላል የሚለውን ጥያቄ የሚመልስ ሰነድ ነው።
ስለዚህ አቶ መለስ ያዘጋጁት ሰነድ ለዚህ ለአዲሱ አመራር ምርጫ ተብሎ ሳይሆን በአጋጣሚ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ የድርጅቱ ሥራ አስፈፃሚ አካላት የተወያዩበት ሰነድ ነበር፤ እሳቸው በህይወት እያሉ በሚቀጥለው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ቀርቦ እንመካከርበታለን ተብሎ ቀጠሮ የተያዘበት ሰነድ ነበር።
ሰንደቅ፡- ስለዚህ ለአመራር ምርጫው ይሄንን ሰነድ በግብአትነት ተጠቅማችኋል ማለት ነው?
አቶ በረከት፡- አይደለም። ሰነዱ ከአሁኑ አመራር ምርጫ ጋር የሚያያዝ ነገር የለውም። ሰነዱ በጠቅላላ በድርጅቱ የአመራር ግንባታ የሚመራበት ሰነድ ነው።
ሰንደቅ፡- የአመራር ምርጫው በምን መልኩ ተከናወነ? የኀሳብ ልዩነት፣ ፍጭት ወይም የጋራ መስማማት ነበር፤ እንዴት ተከናወነ?
አቶ በረከት፡- የኅሳብ ልዩነት አልተከሰተም። የሁሉም ስምምነት የነበረባቸው ጉዳዮች አሉ። በመጀመሪያ ይሄ ጉዳይ ትንሽ ነገር ነው። ኢህአዴግ ትልቁ ኃላፊነቱ ወንበር መከፋፈል አይደለም። የኢህአዴግ ትልቁ ኃላፊነት ሀገር መለወጥ ነው። ስልጣንም ቢሆን በስልጣንነቱ ሳይሆን የሚታየው ሀገር በመለወጥ መሳሪያነቱ ነው የሚታየው የሚል የጋራ መግባባት እንጂ ብዥታ አልነበረም። ስለዚህ ወንበርን ለወንበርነቱ አይደለም የምንፈልገው። ሀገር የሚለወጠው ደግሞ በአንድ ሰው አይደለም። የጋራ ስራ ነው።
ሰንደቅ፡- በአሁኑ ወቅት ከፊት ያለውን አመራር በማየት ቀደም ሲል የነበረው የህወሓት የበላይነት ቀንሷል የሚል ፍራቻ እየታየ ነው፤ ስለዚህ ጉዳይ ምን ይላሉ?
አቶ በረከት፡- በመጀመሪያ ደረጃ በግልፅ የሚታይ ፍራቻ (Frustration) አላየንም። የሚታይም አይመስለኝም። የማይታይበት ምክንያት ህወሓት በአፄ ምኒልክና እና በደርግ እንዲሁም በአፄ ኃይለስላሴ የነበረውን ሥርዓት አምርሮ ሲታገል የቆየው የህወሓት ስርወ መንግሰትን ለመፍጠር አይደለም። ህወሓት የታገለው ዴሞክራሲያዊት የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ነው። ያንን ሁሉ መስዋዕትነት የከፈለውም ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመፍጠር ነው። ስለዚህ ህወሓት የታገለው ምርጫ በዴሞክራሲ አኳን የሚካሄድበት፣ ሀገሪቱ መሪዎቿን በነፃ የመትመርጥበት ሥርዓት እንዲገነባ ነው። ስለሆነም የሰሞኑ የኢህአዴግ ምርጫ የህወሓት የትግል ውጤት ነው። የትግራይ ሕዝብ የትግል ውጤት ነው። የተከፈለው መስዋዕትነት መና እንዳልቀረ የሚያሳይ ነው። እውነት ለመናገር ህወሓቶች በከፍተኛ ደረጃ የኮሩበት ቀን ቢኖር አሁን ነው።
ሰንደቅ፡- ሰሞኑን የተሰጠው የጀነራሎች ሹመት አሁን ካለው አዲስ አመራር ምርጫ ጋር የሚያገናኘው ነገር አለ?
አቶ በረከት፡- ለእኛ ለኢህአዴጎች ይሄ የስልጣን ክፍፍል ምርጫና የመሳሰሉት ነገሮች እጅግ በጣም ትንሹ አጀንዳችን ሆኖ ነው የከረመው። ይሄ ጉዳይ ትልቅ አጀንዳቸው የሆነና እያንዳንዷን ድርጊት ከምርጫው ጋር እያያያዙ ሲያስሩና ሲቀጥሉ የሚውሉ ሰዎች አሉ። ስለዚህ ጀነራል ተሾመ… እያሉ የኃይል ሚዛን ከዚህ ስለሄደ ነው፣ ጀነራል ሲወርድ ደግሞ የኃይል ሚዛን ከዛ ወደዚህ ስለሄደ ነው የሚሉ አሉ። አቶ ኃይለማርያም ከዚህ ስለሆነ ወደዚያ ይሄዳል። አቶ ደመቀ ከዚህ ስለሆኑ ወደዚህ ይሄዳሉ የሚሉ ወሬዎች መበርከታቸውን እንገነዘባለን። ያም ሆኖ አቶ መለስን’ኮ የጋምቤላ ሕዝቦች፣ የደቡብ ሕዝቦች፣ የትግራይ ሕዝብ፣ የኦሮሞ ሕዝብ፣ የአማራ ሕዝብ የሌሎችም ኢትዮጵያ ሕዝቦች አልፎ አፍሪካውያን ሳይቀሩ የእኛ መሪ ናቸው ብሎ ነው የተቀበላቸው። ስለዚህ ይህ ሕዝብ የሚፈልገው የመጣህበትን መሠረት አይደለም፣ የመጣህበትን ብሔር አይደለም። የምትሰራለትን ስራ ነው። ይህ ነገር ያልገባቸው ፖለቲከኞችና አዋቂ ነን የሚሉ ሰዎች ካሉ ችግሩ የእነሱ ነው።
ኢህአዴግ እንደሆነ አቶ ኃይለማርያም ይሁን፣ አቶ ደመቀ፣ አቶ አዲሱ፣ አቶ አባዱላ ገመዳ ወዘተ አንድን ብሔር የሚወክሉ ሰዎች አይደሉም። በአመራር ቦታ የሚቀመጡ ሰዎች በሙሉ በስራ ክፍፍል አንድ ብሔር ላይ እንመደብ እንችላለን እንጂ አንድን ብሔር ብቻ የምንወክል ሰዎች አይደለንም። የመላው ኢትዮጵያውያንን ሕዝቦች፣ ሁሉንም ሃይማኖቶች፣ ሁሉንም ብሔሮች፣ ሁሉንም ጾታዎች፣ ሁሉንም የዕድሜ ክልል በአጠቃላይ አብዛኛውን ሕዝብ እንወክላለን ነው የምንለው።
ሰንደቅ፡- በቀጣይ ግንባሩ የውጪና የውስጥ ተፅዕኖዎችን በምን መልኩ ሊቋቋም ይችላል? በተለይም ከሰሞኑ የዓለም አቀፉ አበዳሪ ድርጅት (አይ ኤም ኤፍ) የሀገሪቱ ጠቅላላ ሀብት ወደ ታላቁ የህደሴ ግድብ እየሄደ በመሆኑ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እየተጎዳ በመሆኑ ግድቡን እንዲቆም የሚል አስተያየት ሰጥቷል። ቀደም ሲል ድርጅቱ ለኒዮሊብራሊዝም አስገዳጅ ሁኔታዎች እጅ እንደማይሰጥ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ወቅት ግፊቱን በግል ክህሎታቸው ጭምር ሲቋቋሙ እንደነበር ይታወሳልና ይሄንን ግፊት በምን መልኩ ነው የምትቋቋሙት?
አቶ በረከት፡- በዚህ ረገድ አዲስ ነገር ፍለጋ የምንሄድበት ነገር የለንም። ባለፉት ሃያ አመታት እንደ ኢህአዴጎች በርካታ ግፊቶችን ስንቋቋም ቆይተናል። ባለፉት ሃያ ዓመታት ሀገራችንን ለመለወጥ ብዙ ሰርተናል። ብዙ መሠረት ጥለናል። በብዙ መስኮችም ለውጥ መጥቷል። በዋና ዋና ሴክተሮች ከአይ ኤም ኤፍ የዓለም ባንክ ምክር ውጪ ሄደን ነው የሰራነው። ለውጪ ባለሀብቶች የባንኩን ዘርፍ ፍቀዱ ሲሉን አንፈቅድም ስንል፣ ቴሌኮሙኒኬሽንን ወደ ግል አዙሩ ሲሉን አይሆንም ስንል፣ መንግስት ከፋይናንስ ሴክተር እጁን ማንሳት አለበት ሲሉ እምቢ ስንል፣ የወለድ ምጣኔ በጣም ከፍተኛ ይሁን ሲሉን ለልማት በሚበጅ መንገድ ነው የምንወሰነው ስንል በአጠቃላይ ከነርሱ ጋር እየተፋለምን ነው የቀጠልነው። ከዚህም በኋላ አዲስ የሚመጣ ተፅዕኖ የለም። ካለም የእነሱንም ተፅዕኖ ለመቋቋም አዲስ የምንዘይደው መላ የለም። በአቶ መለስ ዘመን የነበረውን ሁሉንም ነገር የማስቀጠል ጉዳይ ነው። ልምዱን አግኝተናል። ዛሬ ኢትዮጵያ ማንም መጥቶ እጁዋን የሚጠመዝዝበት ደረጃ ላይ አይደለችም። በጣም ረጅም ርቀት ሄዳለች። በ1983 እና በ1984 ዓ.ም ያልተንበረከከ ሀገርና መንግስት ዛሬ ይንበረከካል ብሎ የሚጠብቅ አካል ካለ ይሄንን ሀገርና የህዝቡን ቁርጠኝነት ያልተገነዘበ ብለን ነው የምንወስደው።
ሰንደቅ፡- ኢህአዴግ ከአመራር ምርጫው በኋላ ለተቃዋሚዎች በጋራ ለመስራት ባስተላለፈው መልዕክት “በጋራ ምክር ቤት ለሚሳተፉ” ብሎ ለይቶ ነው መልዕክቱን ያስተላለፈው። በዚህ ረገድ መድረክን ጨምሮ ሌሎችን ፓርቲዎች ለማሳተፍ አዲስ የቀየሳችሁት አካሄድ አለ? በተለይም ከመድረክ ጋር አብሮ ለመስራት?
አቶ በረከት፡- አዲስ የምንከተለው ነገር የለንም። ከዚህ ቀደም ያስቀመጥናቸው ብዙ ግልፅ የሆኑ ነገሮች አሉ። መድረክ ከእኛ ጋር የነበረውን ድርድር ሲያፋርስ ነው የኖረው። ቁም ነገር ያለው ድርጅት ነው ብለን የምንወስድ ከሆነ በአንድ ዓለም አቀፍ ደረጃ ባለው ስነ-ምግባር መስማማት አለብን። መድረክ ሲያሰኘው አመፅ እየጫረ፤ ሲያሰኘው ደግሞ ጉልበት እጠቀማለሁ እያለ መቀጠል አይችልም። እኛም ለዚህ ኃይል ጫና እየተንበረከክን ልንሄድ አንችልም፤ ሕግና ስርዓት ያለበት ሀገር እንደመሆኑ መጠን ቢያንስ እንደ ፓርቲ ጤናማ መንገድ መከተሉን መረጋገጥ አለበት። ነገር ግን እስከ ዛሬ ይሄ ድርጅት ጤናማ መንገድ ላይ መሆኑን አላረጋገጠም። ስለዚህ የድርድር ኳሱ ያለው በኢህአዴግ ሳይሆን በመድረክ ሜዳ ነው። በመሆኑም መድረክ ራሱን አስተካክሎ ከመጣ ለሁሉም የሚደረገው ይደረጋል። ነገር ግን አመፅን በግማሽ ልቡ እየተመኘና እየሰበከ እንቻቻል ቢል አያስኬድም። መድረክ ለመቻቻል ቅድመ ሁኔታን ሊያሟላ በሚችል ፖለቲካዊ ሁኔታ ላይ አይደለም ያለው።
ሰንደቅ፡- ኢትዮጵያ አሁን ከገጠማት ጊዜያዊ ችግር አንፃር ከኤርትራ መንግስት በኩል የሚደርስ የፖለቲካና የደህንነት ተፅዕኖ ይኖራል ተብሎ ይገመታል?
አቶ በረከት፡- የኤርትራ መንግስት ትንንሽ የመንደር ክፋቶችን ይሰራል። አቅሙም በዛ ደረጃ የተወሰነ ነው። የመንደር ክፋት የሚሰራን አካል የመንደር ክፋት ሰርቶ ጉዳት እንዳያደርስ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል። ከዚህ ያለፈ ግምት የሚሰጠው መንግስት አይደለም። እኛ የኤርትራን መንግስት ወደ መንደር ደረጃ የወረደ መንግስት አድርገን ነው የምናየው::


No comments:

Post a Comment