No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Saturday 1 September 2012

“እንትናም እኮ ሞቱ…!” ከአቤ ቶኪቻው

የጠቅላይ ሚኒስትሩን መሞት ከሚዲያዎች ሁሉ ቀድሞ ያረዳን የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን (ኢሳት) ነበር። በርግጥ ዶክተር ፍስሀ እሸቱ ያዋቀሩት “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሽግግር መንግስት” ከሁሉም በፊት ምሎ ተገዝቶ “ጠቅላዩ ተጠቅልለዋል” ብሎን ነበር። ነገር ግን ይሄ “ብሄራዊ የሽግግር መንግስት” የሚዲያ ተቋም ካለመሆኑ ጋር ተያይዞ ወሬውን ይዞ መምጣቱ እውነቱን ነው አይደለም? ከሚለው ክርክር ይልቅ እንደ ፖለቲከኛ ይሄንን ወሬ ብሎ ማውራት ተገቢ ነው አይደለም… የሚለው መነጋገሪያ ሆኖ ነበር። (ያው የኛ ሰው መነጋገር ይወድ የለ..!? ብለን እንቀጥላለን…)
ኢሳት ወሬውን ካደረሰን በኋላ ግን ብዙዎቻችንን በወሬ ቅብብሎሹ ትጋት አሳየን። በጋተውም አቶ በረከት ስምዖን

በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሽንቁር በኩል ብቅ ብለው አፋቸውን ሞልተው ጠቅላዩ እንደተሻላቸው ነገሩን። በሌላ ንጋታው ደግሞ አቦይ ስብሐት በኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን ስልክ ብቅ ብለው “አቶ መለስ በህይወት አሉ ወይ!?” ተብለው ሲጠየቁ “ከት ከት ከት” ብለው ሳቁ። አንዳንዶች በአቦይ መዝገበ ቃላት መሰረት “ከት ከት ከት” ብሎ መሳቅ “አዎ ነብሳቸውን ይማር ሞተዋል እንግዲህ ምን ዋጋ አለን!” ማለት ነው። ብለው ይፈቱታል። ከዛ ቀጥሎ ነው መሰል፤ አቶ በረከት ውጪ ሀገር ለሚኖር ጋዜጠኛ “ለእንቁጣጣሽ ይመጣሉ!” ብለው አይናቸውን ብቻ ሳይሆን ሁለመናቸውን በጨው ታጥበው ተናገሩ።
በነገራችን ላይ “አርቲስቶቻችን” የጠቅላይ ሚኒስትሩን ለቅሶ ሲደርሱ “ምነው ተለየሽኝ መስከረም ሳይጠባ እንቁጣጣሽ እያልን ሳናጌጥ በአበባ” እያሉ እየዘመሩ የመጡት አቶ በረከት ስምዖንን ለማሽሟጠጥ ነው የሚሉ ወሬዎች እየተደመጡ ነው። እውነትም ካልጠፋ የሀዘን እንጉርጉሮ በዘፈን ለቅሶ የሚደርሱት ለማሸሞር ፈልገው ካልሆነ ሌላ ምክንያት ያላቸው አይመስለኝም።
የሆነው ሆኖ የጠቅላያችን ነገር በተለይም ለኢሳት እና ለእነ አቶ በረከት ወሳኝ ጉዳይ  ነበር። በእግር ኳስ ብናስበው “ኢሊጎሬ” ወይም ፍፁም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ኳስ በእጅ የመንካት ያህል ነበር። እውነትም ሞተው ከተገኙ፤ ኢሳትን “የኢትዮጵያ ህዝብ አይንና ጆሮ” ብለን ልናምነው፤ ሳይሞቱ ከቀሩ ደግሞ አቶ በረከት እንደሚሉት የውጪው ሚዲያ በሬ ወለደ የሚባል ዋሾ የአቶ በረከት ወሬ ደግሞ ላሟ ወለደች የሚባል ሀቅ ይሆናል። ብለን በጉጉት ነበር የምንጠብቀው። በስተመጨረሻም ኢሳት ፔናሊቲውን ከመረብ ጋር አነካካው በረኛው በረከት እዛ ኳሷ እዛ… ደምሴ ዳምጤ ቢሆን ኖሮ “ነቀነቀው…” ይል ነበር። ይልቅ ጋሽ ደምሴ የት ጠፋ…?
ልክ “የት ጠፋ?” ብለን  ስንጠይቅ ከላይ ርዕስ ያደረግነውን ጉዳይ እናገኛለን።
በቅርቡ አንድ ጓደኛዬን ደውዬለት ያው ልማድ ነውና ሳይጠፋ፤ “ምነው ሰሞኑን ጠፋህ?” ብዬ ብጠየቀው “ምነው ውጪ ሀገር ሞተ ተብሎ ተወራ እንዴ!?” ብሎ የውጪ ሀገሩን ሚዲያ አንጓጧል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ እና የአቡኑ መሞት በቅድሚያ ውጪ ሀገር በሚገኙ ሚዲያዎች ተወርቶ እውነት ሆኗል።
ከዛ በኋላ “የለመደች ጦጣ” ሆኖ ነው መሰል ትንሽ ጠፋ ያለውን ሰውን በሙሉ “እከሌ እኮ ሞተ” የሚል ዜና ሲሰራ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አስከሬን ሲሸከም ስናየው፣ አሁንም “እንቶኔ እኮ ሞቱ” ሲባል አስለቃሽ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ስናገኛቸው፣ አሁንም “እንትና ሞተ” ሲባል እየዬ ብሎ ሲያለቅስ ስናየው አነዚህ ሰዎች ስንት ኢሊጎሬ ነው የሚስቱት? ብለን መጠየቃችን አይቀሬ ነው።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት በኢትዮጵያ ላይ ትልቅ ጉዳይ እንደሚሆን አያጠራጥርም። የሼክ መሀመድ አላሙዲን እና የፕሮፌሰር እንድሪያስ እሸቴ ሞት እና ህይወት ግን ለቤተሰቦቻቸው እንጂ ለሀገሪቱ እዚህ ግባ የሚባል ጉዳይ እንዳልሆነ “አስመልክቶኛል” እንኳንስ ሌላው ቀርቶ ጀነራል ሳሞራው የኑስ ራሳቸው ሞቱም አልሞቱም ብዙም ተፅዕኖ ማሳደራቸውን እንጃ…!
እነዚህ ሶስት ሰዎች በየተራ በርግጠኝነት እንደሞቱ በውጪ ሀገር ሚዲያዎቻችን የተነገረባቸው ናቸው። የዚህ ወሬ ጥቅም ምን እንደሆነ እንጃ… በነገራችን ላይ አንድ ምስጢር እንኩማ…
አንዳንድ ጊዜ ዋና የስራ ሂደት ባለቤቶች “የፉገራ” ወሬ “ከውስጥ ያገኘሁት መረጃ ነው ስሜን ሳትጠቅስ ተጠቀምበትማ…” በማለት “ሹክ” ብለው “ማኖ” እንደሚያስነኩ ሰምተናል። ለዚህም “ብሉሀኖች” ምን ታማኝ ምንጭ ቢሆን፤ ድንጋይ አስነክሰው ካላስማሉ በስተቀር ለህዝብ ይፋ እንደማያደርጉ ነግረውናል።
ስለዚህ ሞተ ለማለትም ሆነ፣ ኮበለለ ለማለት፣ እንኳንስ ሌላው ቀርቶ “ሲንግል” ለቀቀ ለማለትም ቢሆን መረጃ የሚያቀብሉንን ሰዎች በአባታቸውም በአያታቸውም ስም አስምለን ካልሆነ ላለማስተጋባት ቃል መግባት አለብን! አለበለዛ ይሄንን ሁሉ “ፔናሊቲ” ስንስት የተመለከቱ ታዛቢዎች ከዚህ በኋላ በረኛ በሌለበትም አያገቡም ብለው ተስፋ እንዳይቆርጡብን ያሰጋል።
በነገራችን ላይ አቶ ተፈራ ዋልዋም እስካሁን በለቅሶው ላይ አልታዩም… አሉ… “ሞተዋል ብላችሁ ዜና እንዳትሰሩ ገዝቻለሁ!”
በናታችሁ ታማኝ እንሁን!

No comments:

Post a Comment