No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Tuesday 28 August 2012

የኢትዮጵያን ሕዝብ ማቅ አልብሶ በብሄራዊ ሃዘን ስም እያስገደዱ ማስለቀስ ገደብ ይበጅለት!

የጐንቻው!
በኢትዮጵያ ቤተመንግሥትና ቤተ መቅደስ ባሳለልፈነው ሳምንት የተፈጸመውን እጅግ አስደናቂ መቅስፍት ( የአባ ጳውሎስ እና የጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ህልፈተ-ሞት) ቋንቋ ሊገልጸው በሚችለው መንፈሳዊና ፓለቲካዊ ትንተና ጠቢባን፤ሊቃውንት፤ ወጣት፤አረጋዊት፤ምዕመናን ሁሉ እንደየስሜታቸው የተገለጸላቸውን ያህል የሚፈላሰፉበት፤ የሚደሰኩሩበት፤የሚቃኙበትም እጡብ ድንቅ ክስተት ነው።
ለ21 ዓመት በኢትዮጵያ ቤተመንግሥት በትረ ስልጠን የተቀመጡት አቶ መለስ ዜናዊ ሕመማቸው ከኢትዮጵያዊያን በረቀቀ በሚስጥር ተደብቆ ሲያወዛግብና ሲያደናብር ከርሟል፤በሰበቡም ሃገሪቷ የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ በሚል የሞኝ ብሂል መንጋዎች ለባሰ ዝርፊያ ተጋልጣ በአየር፤በመኪናናን በግመልም እየጫኑ ሰርቀው ወደ ባዕድ ሃገራት በሚያሸሹ ቀማኞች እርቃኗን ቀርታ በብሄራዊ በባንክ ያለው የውጭ ምንዛሬ ገንዘብ ሳይቀር ተሟጦ እንደነበር በይፋ የተነገረ ለወደፊቱ የሃግራችን የንግድና

የኢንቨስትመንት ደንበኞች የሚያስፈራ፤ ህዝቧንና ኢኮኖሚውያን በእጅጉ የሚጎዳ ብሄራዊ አደጋ ነው።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ የህዎትና የጤና ሁኔታ በመንግሥት ባለስልጣናትና ደጋፊዎቻቸው በኩል ይሰጥ የነበረው ማሰተባበያና ክህደት ለዘላዓለም የሚያስተዛዝብ ቅጥፈት ሆኖ ሰንብቷል። ውሸት እንዴት በመንግሥት መዋቅር ከኤይድስ የከፋ በሽታ እንደሆነ ደጋግመን ሰምተናል፤አይተናል። ይኸንን የፈጸሙ ሁሉ ለሕዝብና ለሃገር ሃላፊነት፤ታዓማኒነት የሚይበቁ ከሃዲ ናቸውና በራሳቸው ጊዜ ውሸታቸውንም ቢሆን ሞተው ቢሰወሩ ይሻላል።
በእነሱ ቤት ብልጥ ሆነው የኢትዮጵያን ሕዝብ ባይታወር አድርገው እራሳቸውና ከባዕዳንም ጭምር በሚስጥር ሲመክሩ ከርመው፤የተጣጣፈ የኃይዎት ታሪክ ለሁለት ወር ሲደርቱ ነበር። ይሁናና ነሃሴ 20 ቀን 2012 በይፋ ሲገልጹልን ትናንት ማታ 11:40 ላይ አቶ መለስ ድንገት አረፉ አሉን።
የኢትዮጵያ ሕዝብ አንዳች ነገር እንዳያውቅ ተደርጐ በተገላቢጦሽ ስለ ብልሁና ታታሪው መሪ የተሟላ ጤንነትና እረፍት ሲሰበክለት ከርሞ አቡክተው የጋገሩትን ሚስጥር እንደዘረጉ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስከሬን ቦሌ ገብቷልና በየመንደሩ ዳራቻ ቆማችሁ ቆዝሙ፤የደፈሩትን የአባይ ኃዳሴ ግድብ የሚሞላ እንባ አጉርፋችሁ ካላወረዳችሁ ብለው አይን የሚጠነቁሉ ነጭ ለባሽና አጋዚ ሰራዊት አሰማርተው ሕዝቡ ፊት ለፊት አፍጠውበታል።
ከትንሽ ቀናት ቀደም ብሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ፓትሪያሪክም አባ ጳውሎስ (ገ/መድህን) የአቶ መለስ የጐጥ ልጅና መንትያ እንዲሁ በድብቅ ስለደህንነታቸውና ሙሉ ጤንነታቸው እስከ ደቂቃ በመሃላ በሚመሰክሩ ‘መንፈሳዊ ግብር አበሮቻቸው’ እየተነዛ ሳለ የህይዎታቸው ኃልፈት ደርሶ የመርዷቸው ጩኸት የአጠሩትን የሚስጥር ገደብ ዘልቆ የተስተጋባው የዋይታ ጩኸት እንደ ገደል ማሚቶ በያለንበት መርዶውን አበሰረን።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ይኸንን ድርብርብ ትዕንግርት በልቦናው፤በህሊናው መዝግቦ በውስጡ እያነበነበው ይገኛል፤ምናልባትም የጉዳይና የሚስጥሩ ባለቤት ፈጣሪ አምላክ ሳይሆን አይቀርምም ብሎም ያምናል። ታዲያ ከሕገ-መንግሥቱ፤አንቀጽ፤ከፓርቲው የፓለቲካ ፕሮግራም አለያም ከሲኖዶሱ ደንብ ተጠቅሶ በሰው አንደበት ከሚገለጽ በላይ ነውና። እያንዳንዱ ምዕመናን ግንኙነቱ እንደተገለጸለት፤እንደ ስሜቱ ከዚሁ መንፈሳዊ ሃይል ጋር ተጎዳኝቶ ዓይኑን ጨፍኖ፤አፍጦም የድርጊቱን ትልቅ ታዕምራዊ ክስተት የረቀቀ መልዕክት ተገንዝቦ በትዕግስት ድባብ ተደምሟል።
ኢትዮጵያውያን ፍጹም ጨዋ የሆነ ባህል መሰረት ለሟቾቹ አዝኖ አልቅሶ ሲቀብር፤ በክብር ሲሰለፍ ወያኔዎች ግን ፓለቲካዊ ትርፍ ሊሸቅጡበት ዘመቻ ከፍተዋል። ይኸ ያስነሳው ጦስ በየጐራው ከስንኝ እስከ ዳጎስ ያለ መጣጥፍ እያስከተበ በኢንተርኔትና በተለያዩ ሚዲያዎች ሰጣ ገባው ተጧጡፎ፤ አታካሮ ቀዝቃዛ ጦርነት አስነስቷል።
ዋናው እውነታ ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሰው ሕይዎት ትልቅ ዋጋና፤ክብር ይሰጣል። ሞትንም እንደ ሕይዎት ክብር ይሰጠዋል፤ በቆየ ባህሉ ደመኛው (ባላንጣውንም) ሳይቀር ሲሞት ክፉውን ሁሉ ለአምላክ ፍርድ ትቶ በደግ ይቆማል፤ይቀብራል፤ያጽናናል።
ዛሬ የሁለቱን የስርዓት ቁንጮዎች ታዕምራዊ ሞት ተከትሎ የሚብሰከሰኩትን ጭፍን ደጋፊዎች ሁኔታ ከሃዘን ባለፈ ይባሱን እነሱ በተለይ የተበደሉ፤የተገፉ፤የተከፉ፤አድርገው እራሳቸውንና ድርጅታቸውን አንቀሳቅሰው በሌላው ኢትዮጵያዊ ወገን ላይ የጥላቻ፤የጥፋት፤የቂም በቀል መርዝ ፤እርካሽ ስድብና የእብሪት ቁጭት ሲያንገበግባቸው ይስተዋላል። ይኸ መቸም የጤና አይመስልም።
የኢትዮጵያ ሕዝብ እኰ አቶ መለስ ዜናዊ በሚያዝዙት መንግሥትና ሰራዊት፤አባ ጳውሎስ በሚሰብኩበት ቤተመቅደስ ከግራና ከቀኝ እንደ ሲዖል እየተገረፈ፤እጅግ ፋሽስታዊ የግፍ ጭፍጨፋ የደረሰበትን አበሳ ገና ወደ ፊት በታሪክ ስንክሳር እንደተራራ ወጥቶ የሚቆለል ገሃድ አለው።
ይሁንና እልክ አስጨራሽ በሆነ አስከፊ 21 ዓመት ሲኖር ብዙ የመከራ ገፈታ ቀምሷል፤በዚህ ጨካኝ ሥርዓትና ደጋፊዎቹ፤ 2005 ላይ በአገራችን መዲና ሁለት መቶ ሰላማዊ ዜጐችን በየአውራጎዳናው በመሳሪያ አነጣጥሮ ያስጨፈጨፈ ሲሆን ከአንድ ሺህ በላይ ከፍተኛ ማቁሰልና አካል ማጉድለ አድርሷ፤ከ40ሺህ በላይ ሰላማዊ ዜጐቹን ደግሞ እንደ እቃ ጭኖ አፍሶ በማጋዝ አይቀጡ ቅጣት አድርሷል።
ታዲያ ዛሬ ከአየር መንገድ ጀምረን ተሰለፍን የእንባ ሃይቅ ገድብን አስከሬናቸው በትንሿ የኖሕ መርከብ እየተቀዘፈ እንደ ሰላም እርግብ፤እንደ መልዓክ እስኪያርጉ አምጣችሁ አንቡ ተብለናል። እየተዎራጩ አብሬ ካልተቀበርኩ ሃዜና አይወጣልኝም ከሚሉት እመቤት አዜብ ጋር ያወዳድሩናል። እመቤቷም ሆኑ በተለይ ልጆቻቸው ባል፤አባታቸውን እንዲያጡ የሚመኝ አይኖርም፤ ይሁንና እኒህ ቤተሰቦች ከላይ ያወሳሁትን የ2005 ዓም ሰቆቃና ጭፍጨፋ በቀጥታ ትዕዛዝ አስፈጽመው በአዲስ አበባና በመላ ሃገሪቱ የከፋ የመከራ ደመና አንዣቦ ህዝብ ደም እያለቀሰ፤የእንባና የደም ጐርፍ እየወረደ፤ የልዕልት ልጃቸውን የልዕደት በዓል በሸራተን ደግሰው በሙዚቃና ዳንስ ይቀማጠሉ እኰ ነበር። ማንም ሰብዓዊ ፍጡ ያደርገዋል ተብሎ የማይታሰብ ገመናና ጉድ አላቸው።
አቶ መለስና አባ ጳውሎስ ነግሰው፤ፐትርከው፤ከብረው፤ዙፋን ወርሰው አውርሰው፤ ብዙ ቢሊዮን ዶላር በአለም ባንክ አጭቀው ለዚያ ካበቃቸው መቶ ትውልድና ጐጣቸውንም በችግር ጊዜ የሚያወላዳ ካዘና ሞልተውላቸው ነው በ57 አና በ76 ዘመናቸው ኑሮን አጣጥመው የሞቱት። አባ ጳውሎስም ሃውልታቸውን በእንቁ ድንጋይ አንጸው፤ድርብርብ ሥጋዊ ምቾት ተጎንጽፈው በእድሜ ጃጅተዋል። በቅርቡም የ20 ዓመት ድግስ ሸራተንን ጨምሮ ሦስትና አራት ቦታ ድል ያለ ግብር ጥለው ለሚወዷቸው ሁሉ አብልተው፤አጠጥተው ሂሳቡን ለኛ ትተውልን ነው ዓለም በቃኝ ያሉን።
እነርሱ የገደሏቸው/ያስገደሏቸው፤ያሳደዷቸው፤ያሳሰሯቸው እልፍ ዜጐቻችን፤ሕጻናትና ወጣቶች በለጋ እድሜያቸው የተቀጩ፤የኑሮንና የሕይዎትን ትርጉም በጅምር የተቀሙ፤ወይም ቤተሰብ በትነው የግፍ ሰለባ የሆኑ አባዎራዎችና እናቶች ናቸው። ወገን ቤተሰባቸው ዘላለም ጨልሞባቸው እስካሁና ደቂቃ እንባቸው አልታበሰም።
ታዲያ በተገላቢጦሽ በተከሰተው ‘አነባበሮ ሞት’ ሆድ ብሶናል ብለው ተጨማሪ 21 ዓመት ተካክሰው ቀጥቅጠው ካልገዙን አንረካም እያሉ ሚሾ የሚጠሩት በቅጡ ይሁኑልን።
ለመሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሞት ድንገት ሸወደው እንጂ እኮ እኒህ ያስቃዩትን ግፈኞች ጸንቶ ሲታገልና በድሉም አፋፍ ላይ ደርሶ ወንጀለኞቹን ሁሉ በህግ ሊፋረድ እንደ ግብጹ ፕ/ት ሙባረክ ከተኙበት የሆስፒታል ሳንሳ ጭምር ሊፋረዳቸው የቆረጠ እንደነበር አያውቁም ይሆን። ለዚህም ይመስለኛል ሁሉ ነገር ሚስጥርና ድብብቆሽ የሆነው፡ ይሁንና አምላክ የራሱ ዘዴ ኖሮት ምናልባትም ብዙ ደም መፋሰስ አልፈለገ ይሆናል እሱ ስራውን ሰራ። ይኸንን የማይገነዘቡ በራሳቸውም መቅሰፍት የሚጋብዙ ናቸው።
በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የተፈጸመ እጅግ ከመጠን ያለፈ ግፍ አለ፤ ሞት የማይቀብረው፤የማይሽረው፤ ወንጀል፤ነውና፤ በሞት ካሳ በደላችንን ሁሉ እንደንረሳ የከፈቱብንን ዘመቻ ቢያቆሙ ይበጃል።
ጠቅላይ ሚኒስሩ በሕይዎት ዘመናቸው ጥይት በማይበሳው መኪና ተጭነው በአውራ ጎዳና ሲያልፍ ሲያገድሙ እንኳ ሕዝቡ ፊቱን ወደ እርሳቸው አቅጣጫ እንዲያዞር የሚይፈቀድለት፤ሺህ ሜትር ርቆ እንዲቆም በገዳይ አጋዚዎቻቸው የሚቀጠቅጡት፤ የሚያባርሩት ሕዝብ እኰ ነበር ዛሬ እሬሳቸውን አማትበህ አልቅስ የሚባለው።
99.6% እንኳ መረጠኝ፡ብለው ደስታቸውን ‘በሚወዳቸውና፤በሚወዱት ሕዝብ’ ፊት መስቀል አደባባይ ለመግለጽ ሲቀርቡ በከባድ መሳሪያ ታጅበው፤መድፍ በማይበሳው የመስተዋት ቁም ሳጥን መሽገው እንደ ቴሌቪዥን መስኮት አፍታ ብቅ ብለው ነበር የሚሰወሩን። የማይወዱትን፤የሚገሉትን፤የማያምኑትን ሕዝብና የሚያጠፏትን ሃገር አናት ላይ ተፈናጠው የሚገዙት ሰው፤እኮ ነበሩ። ታዲያ ዛሬ ተናዘው ነው? ወይስ ፈጣሪ የሕዝብ አስተያየት ጠይቆ ነው እንዲህ አስከሬናቸው በግላጭ በየበረንዳው፤በየመንደሩ ጨርቅ ባሉት ባንዲራ አሽሞንሙነው እንደ ሎቶሪ እያዙሩ መሪሪ አዘናችሁን ትወጡ ዘንድ የቀረውን እድሜያችሁን ማቅ ለብሳቹህ ስታለቅሱ፤ስታነቡ ኑሩ የሚሉን። እንደ እኔ እምነት ከሆነ አቶ መለስ እንዲህ በግልጥ ወደ ሕዝብ መቅረባቸውን ቢያውቁ እንዴት እንዲሚደነግጡ ይታየኛል። ሕዝቡ ክብሪት ጭሮ ከሲዖል በከፋ እሳት እንደሚለበልባቸው ይሰጋሉ።
ይባስ ብሎ በመንግሥትና በፓርቲ መዋቅር የሃገሪቱ ዋነኛ ሥራና ቀዳሚ ተግባር ተደርጎ ከቀበሌ እስከ ክልል ድንኳን ተጥሎ ከእያንዳንዱ የሚነጥበው እንባ በደህንነትና ነጭለባሽ ሰራዊታቸው እየተለካ ይገመገማል። ድንገት እንባ ያጠጠው ቢኖር ከመገረፍ፤መታሰር፤እስከ ሥራ መባረር ይገጥመዋል። ያለ አበሳው በእሥር ቤት ለ18 ዓመት የሚያማቅቁት የተቃዋሚ ፓርቲ
መሪ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዜርን አለማልቀስ ተከትሎ በእስር ቤት ጠባቂ ሕይዎቱን ስጋት ላይ እስኪጥል የደረሰበትን ድብደባ ልብ ይሏል።
የአቶ መለስ ቋሚዎች ግን አሁን የሚጨነቁት ለእርሳቸው አይደለም፤ቢዋጣላችው ደራርተውም ቢሆን የእርሳቸውን ምስል (ጉፍል) ወጣጥረው እያንቀሳበሱ በመስተዋት ወይም በቴሊቢዥን ድምጻቸውን ኮርጀው የዓዲስ ዓመት ምኞታቸውን ቢያዥጎደጉዱልን 11.% ጠግበን እንባጅ ነበር። ያ አልሆነምና እንዲህ ሕዝቡን የሆድ ብሶቱን ቆስቁሰው፤ቁስሉን እየነካኩ ሌት ከቀን እያስለቀሱ እነሱ ሌላ መሰሪ ሥራቸውን ‘ተሰይመው’ እየሰሩ ናቸው። ጭንቀታቸው እንዴት መንበረ ስልጣናቸውን በበለጠ አጠናክረው ለብቻ እየገዙን እንደሚኖሩ ነው።
አሁንማ ወደ ውጭ አገርም በዲፕሎማቲክ ደረጃ መመሪያ ተላልፎ የአስከሬናቸው አምሳያ (ሬፕልካ) እንደ ኦሎምፒክ ችቦ ዓለምን ሳይዞር አይቀርምና እንባችሁን ቆጥቡ። ይህ ሁሉ ከመጠን ያለፈ እብደት ነው፤
ይልቅስ ከዚህ ታምራዊ ክስተት ሁሉም ተምሮ፤ተማምሮ አገራዊ እረቀ-ሰላም እንዲወርድ የማመቻቸትና የማቀራረብን ሥራና በር ቀድመው ከፍተው ሃሳብ ማስተናገድና ስትራቴጁ መንደፍ ይኖርባቸው ነበር። ታጋሹ ሕዝብ ሟቾች አፈር እስኪለብሱ እያሰተዛዘነ፤እያለቀሰ፤እያጽናና ቢቆይም ይኸንን ጉድ ግን እየታዘበ መሆኑን አይውቁ ይሆን? ገፍተው ከተመናቸኩ፤ ውሎ አድሮ መፋጠጥ ይመጣል፤ ያኔ የሚያለቅሰውን አምላክ ያውቃል።
ከዚህ በኋላ የዛሬ 21 ዓመት ጊዜ ሎቶሪ አውጥቶላቸው ሰተት ብለው ቤተመንግሥት ገብተው፤የጨበጡት በትረ ስልጣን እንደ ሱስ አስክሯቸው አይናቹህን ጨፍኑና እናሞኛችሁ የሚሉ ከሆነ አጋጣሚውን ያልተጠቀሙ ቂሎች እነርሱ ናቸው። ‘የወጋ ቢረሳ፤ የተወጋ አይረሳም’ ወገን ነቅተህ ጠብቅ፤ፍጹም መዘናጋት አያስፈልግም።
ወያኔን ጭምሮ የሚያዋጣው ተግባር ለሁላችን የምትሆን አገር፤ኢትዮጵያንና የሁሉንም ዜጋ መብት የሚያስከብር ዲሞክራሲያዊ ሥር ዓት በጋራ መገንባት ነው።
ይኸንን የተቀደሰ አማራጭ በበጐ ለመመለስ አሁን ኳሷ ያለችው፤በወያኔ ሜዳ ላይ ነው።
የጐንቻው! yegonchaw@yahoo.co.uk 25.08.12

No comments:

Post a Comment