No one is born hating another person because of the colour of his sikn, or his background or his religion.
People must learn to hate, and if they can learn to hate, they can
be tought to love, for love comes more naturally to the human heart than its opposite. Nelson Mandela.

Monday 9 September 2013

በስዊድን ጉተንበርግ ከተማ ሊደረግ የታሰበው የዓባይ ግድብ የቦንድ ሽያጭ ከሸፈ (ቪዲዮ አለው!)

ተቃዋሚው ከሰላሳ ደቂቃ በኋላ መድረኩን ተቆጣጠሮ ያዘ (ቪዲዮ አለው!)
 

“ይገርማል!” ብሎ መጀመር ይቻላል። አዎን ይገርማል! ከስቶክሆልም የሄድነው ወደ አዳራሹ የገባነው ጥሪ ባደረጉበት 13፡00 ሰዓት ነበር። እ.ኤ.አ ኦገስት 31 ቀን 2013.። ህዝቡ እስኪሰባሰብ ጥቂት ከተጠበቀ በኋላ ስብሰባው በአንድ የኢህአዴግ/ወያኔ ካድሬ ተከፈተ። እንዲህም አለ፤ “እዚህ እኛን ለመቃወም የመጣችሁ እንዳላችሁ እናውቃለን። ሃሳባችሁን እንድትናገሩ አንከለክልም፤ ነገር ግን ጩኸት፣ አላስፈላጊ ረብሻና ግርግር የምትፈጥሩ ከሆነ ወዮላችሁ! አስቀድመን ባዘዝነው የፖሊስ ኃይል እየተለቀማችሁ ትወጣላችሁ። መውጣታችሁ ብቻ አይደለም፤ ታሪካችሁ ይጠፋል፣ ውርደት ይከተላችኋል። በመለያ ቁጥራችሁም ላይ የሚጻፈው ወንጀል ዕድሜ ልካችሁን ይከተላችኋል።”
ንግግሩ ለሱማልኛ ተናጋሪዎች በአስተርጓሚ ተነገረ። ካድሬው ንግግሩን ቀጠለ “… ወደምሳ ትወጣላችሁ ከዛ በኋላ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ የመጡ ተወካዮች ንግግር ያደርጋሉ። የቦንድ ሽያጩም ሥርዓት ይቀጥላል።” ከካድሬው ንግግር በኋላ በቀጥታ ወደምሳ ተወጣ፤ ለተቃውሞ የመጣው ነጠል ነጠል እያለ ምክክር ያዘ፤ ምሳ የሚታሰብ አልነበረም። በካድሬው ንግግር ሁሉም አንጀቱ ጨሷል እዚህ እንዲህ የተናገሩ የሀገር ቤት ወገኖቻችንስ እንዴት ይሆኑ? ሁሉም የሚያስበው ይሄን ነበር።
ምሳ እየተበላ እያለ በርከት ያሉ የሙስሊም እምነት ተከታዮች፣ የኦሮምኛ ተናጋሪዎች እና ሌሎችም ወገኖች ወደ አዳራሹ ገብተው ከተቃዋሚው ጎራ ጋር ተቀላቀሉ። ሌላውም ምሳውን እየጨረሰ ወንበሩን ያዘ።
የበፊቱ የኢህአዴግ/ወያኔ ካድሬ አሁንም መናገሪያውን ጨበጠ። “እንኳን በሰላም መጣችሁ! … አሁንም በድጋሚ ልናገር የምፈልገው ማንኛውም አይነት ጩኸት፣ ረብሻና ግርግር ውርደት ማስከተሉን ነው። እዚህ ከምታዩት የጥበቃ ኃይል በተጨማሪ ፀጥታ ለማስፈን የተዘጋጀ የፖሊስ ኃይል በመኖሩ ትዕዛዝ ሲሰጠው ወዲያውኑ ሥራውን እንደሚጀምር ልነግራችሁ እወዳለሁ። ሁለተኛ፤ ማንም ሰው ካሁን በኋላ በሞባይል ቴሌፎንም ሆነ በካሜራ ምስል መቅረጽ አይችልም።” ይህ ንግግር ለካድሬው የመጨረሻ ነበር የሆነው።
በተቃውሞ ወገን ያሉ ወገኖች ድምፃቸው ማሰማት ጀምሩ። “ስብሰባውን እየበጠበጥክ ያለኸው አንተ ነህ አታስፈራራን፤ መቅረጽ መብታችን ነው፤ ይህ የነፃነት ሀገር ነው፤ ማንም መብታችንን ሊገድብ አይችልም፤ …” ቀረጻ ተጀመረ ካድሬው ከጠበቀው በላይ ተቃውሞውና ተቃዋሚው መብዛቱን በማየቱ በድንጋጤ ተዋጠ። ወድያውም አንድ ለኢህአዴግ/ወያኔ የቆመ ግለሰብ አንዱን የተቃዋሚ ወገን በመማታቱ ሁሉም ብድግ ብሎ ወደሰውዬው ተወረወረ፤ ወንበሮች ተነሱ ረብሻና ግርግር ሆነ። ወዲያውም የጥበቃ አባሎች ገብተው ነገሩን አረጋጉት። ከዚህ በኋላ ግን መድረክ መሪውና የኢህአዴግ/ወያኔ ደጋፊዎች የት እንደገቡ አልታወቀም፤ ጠፉ ማለት ይቀላል።
ይህ የሆነው ስብሰባው ከተጀመረ ሰላሳ ደቂቃ በኋላ ነበር። አሁን መድረኩን ተቃዋሚው ተቆጣጥሮታል። እንደተባለው በርካታ የፖሊስ ኃይል ወደ አዳራሹ ገባ። ሄሊኮፕተር አካባቢው ላይ እያንዣበበ መቆጣጠር ያዘ። ተቃዋሚው የራሱን መፈክር ለጠፈ። ባንዲራውን በሌላ ባንዲራ ቀየረ። መፈክሮች ማሰማቱን ቀጠለ። “ከዓባይ በፊት ዘረኝነት ይገደብ! ከዓባይ በፊት በግፍ የታሰሩት ይፈቱ! ከዓባይ በፊት ሰብዓዊነት ይቅደም! የህዝብ መብት ይከበር! … ድምፃችን ይሰማ! መሪዎቻችን ይፈቱ! ንጹኀንን መግደልና ማሰር ይቁም! መንግሥት ከኃይማኖት ላይ እጁን ያንሳ! …” ሌሎችም መፈክሮች ተሰሙ።
ከዚህ በኋላ ተቃዋሚው የራሱን ስብሰባ ማካሄድ ጀመረ። በከተማው ላይ ለሌላ ግዜ አብሮ ለተቃውሞ የሚንቀሳቀስ ግብረ ኃይል አቋቋመ። በየጊዜውም በማንኛውም ቦታ ጥሪ ሲደረግ ለመገናኘት ተስማማ። በተቃውሞ ከመጡትና ካስተባበሩት ተቃዋሚዎች መካከል አንዱ፤ “ወገኖቼ! በሀገራችና በህዝቡ ላይ የሚደርሰው ግፍ አስቆጥቶአችሁ ከየቦታው በመምጣት ይህንን ለማድረግ በመቻላችሁ ከፍታኛ ኩራት ተሰምቶኛል። ተቃውሞአችን በዛሬ ብቻ አያበቃም። ገና ይቀጥላል ከሀገራችን አሰድደውናል። እዚህም ደግሞ እያስፈራሩ ናቸው። ይህን ዝም ብለን አናይም፤ መከላከል አለብን። አላግባብ የታሰሩትንም ማስፈታት የኛ ኃላፊነት ነው።” ሲሉ ተደምጠዋል። ሌሎችም ንግግርና መፈክር ያሰሙ ሲሆን በተለይ ሴቶች እህቶች በከፍተኛ ወኔና ቆራጥነት ድምፃቸውን አሰምተዋል።
ከዚህ በኋላ እስከ 19፡00 ሰዓት ድረስ የስብሰባው አዳራሽ የተያዘ ስለሆነ እስከዛ መቆየት ይገባናል በማለት ተቃዋሚው ቢስማማም፤ የፖሊስ አባላት ከዚህ በኋላ እነሱ እንዲሰበሰቡ አናደርግም በማለታቸው ተቃዋሚው አዳራሹን ትቶ መፈክሮቹን እያሰማ ለመውጣት ችሏል።
በዕለቱ የታየው ሁኔታ የኢህአዴግ/ወያኔን አባላትና ደጋፊዎቹን ያሸማቀቀ፤ የተቃዋሚውን ወገን ያኮራ ሲሆን፤ ስብሰባው በአስገራሚነት ተጀመሮ በአስገራሚነት ተጠናቅቋል።
http://www.ethiopiazare.com/

No comments:

Post a Comment